ከኢትዮጵያ አየር መንገድ በማንነታቸው ምክንያት ተባረዋል፤ በግፊት ስራ ለቅቀዋል፤ ተሰቃይተዋል!

ከአራት አመት በፊት ነው። ለአየር መንገድ ሰራተኞች አንድ ኢሜል ይደርሳል። የመልዕክቱ ይዘት እነ ተወልደን ይመለከታል። የአንድ ጎጥ ሰዎች በአየር መንገዱ ላይ የሚሰሩትን የሚገልፅ ነው። ለሰራተኞቹ ለደረሰው አንድ መልዕክት 24 የአየር መንገዱ ሰራተኞች “እናንተ ነው የፃፋችሁት” ተብለው ስቃያቸውን አዩ። የአየር መንገድ ደሕንነቶች ሰራተኞቹን አዋከቧቸው። ስቃይ አሳዩዋቸው።

ሰራተኞቹ “እኛን ፈፅመናል ካላችሁ ማስረጃ አምጡ” ብለው ሞገቱ። ምንም አይነት ማስረጃ አልነበረም። እንዲያውም በሌለ ማስረጃ “በሽብር ወንጀል ከስሰን 18 አመት እናስፈርድባችኋለን” ብለው ዛቱባቸው። ይህን ለማለት ምንም አይነት ማስረጃ አልነበራቸውም።

ሰራተኞቹን በደሕንነት ሲያሰቃዩም ምንም ማስረጃ አላገኙም። በመሆኑም ሌላ መንገድ ጀመሩ። “ከአስር አመት በላይ ስለሰራችሁ፣ አምናችሁ ይቅርታ ከጠየቃችሁ በስራችሁ እንድትቀጥሉ እናደርጋለን” ተባሉ። “ምንም ባልሰራነው ነገር ይቅርታ አንጠይቅም። ወይንም ይህን ሰራችሁ ብላችሁ በፅሁፍ ግለፁልን” አሏቸው። በፅሁፍ መግለፅ አልፈለጉም።

ሰራተኞቹ “ምንም ያጠፋነው ነገር የለም፣ ወንጀል ሰርታችኋል ካላችሁ ማስረጃ አቅርቡ፣ ባልሰራነው ነገር ይቅርታ አንጠይቅም” ሲሉ ከቦታቸው እያነሱ የማያውቁት ቦታ አስቀመጧቸው። ተማርረው እንዲለቁ ነው። ወደ ውጭ የሄዱትም እንዳይመለሱ ተደረጉ። “ኢሜሉን ፅፏችኋል” ከተባሉት መካከል አንዲት የትግራይ ልጅ ብቻ ይቅርታ ጠይቃ በስራዋ ቀጠለች!

በአየር መንገዱ ላይ የሚነሳው ነገር ብዙ ነው። በርካቶች በማንነታቸው ምክንያት ተባረዋል። በግፊት ስራ ለቅቀዋል። ተሰቃይተዋል!