ፖሊስ ዶላር በጥቁር ገበያ ሲሰበስቡና ከሐገር ሲያወጡ ደረስኩባቸው ያለውን የሕወሓት ሰዎች በቁጥጥር ስር አዋልኩ አለ

አሸባሪው የህወሃት ቡድን ከአዲስ አበባ እስከ ቶጎውጫሌ በዘረጋው ህገ-ወጥ የዶላርና የገንዘብ ዝውውር ኔትዎርክ፣ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ሰነዶችና ገንዘቦች ከነተጠርጣሪዎቹ መያዙን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ገለፀ፡፡
ዶላሩን ከአዲስ አበባ በጥቁር ገበያ እየሰበሰበ መንግስትን እንዲዳከም ሲሰሩ የተደረሰባቸው መሆኑን አቶ ዮናስ ማሞ ጠቁመዋል፡፡ አሸባሪው ቡድን ቀድሞ በሰራው ኔትዎርክ አማካኝነት በንግድ ተቋማት የሚሰበሰቡትን ዶላሮች በሀገ-ወጥ መንገድ ከሀገር እንዲወጣ በማድረግ ለሽብር ቡድኑ ዋነኛ የፋይናንስ ምንጭ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ፖሊስ ከወንጀል ድርጊቱ ጋር ቀጥተኛ ተሳትፎ አድርገዋል ያላቸውን 6 አለም አቀፍ የገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶችና 11 ግለሰቦች ከ14 ባንኮች የተከፈቱና አስር ሚሊዮን ሁለት መቶ ሰባ ስድስት ሺህ አራት መቶ ዘጠና ስድስት ብር ከያዙ ከመቶ በላይ የባንክ የሂሳብ ደብተሮች ጋር በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ መጀመሩን አስታውቋል፡፡
 የህወሃት ቡድን በአዲስ አበባ ህጋዊ አሰራርን ሽፋን በማድረግ መንግስት እንዲዳከምና ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ ለሚያስገባቸው ጥሬ እቃዎች የዶላር እጥረት እንዲያጋጥመው እንዲሁም የኑሮ ውድነትን አባብሶ ህዝብ በመንግስት ላይ እንዲነሳ ለማድረግ የሞከረ መሆኑንም ፖሊስ ድርሼበታለሁ ብሏል፡፡ አሸባሪ ቡድኑ በውጭ ሀገር ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎቻቸው ገንዘብ በመሰብሰብ ለጦር መሳሪያ ግዥና ለባለስልጣናት ልጆች ትምህርት ቤት ወጪ ያውሉታል ተብሏል።
የሽብር ቡድኑ በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጫና በመፍጠር የኑሮ ውድነት እንዲባባስ ማድረጉም ተነግሯል፡፡