በባሕር ዳር በብአዴን የውይይት መድረክ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች

በብአዴን የውይይት መድረክ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች

• ለዘመናት በመልካምም ሆነ በፈታኝ የታሪክ አጋጣሚዎች ሁሉ አብሮነት እና መቻቻል የሀገራችን ህዝቦች አይነተኛ እሴት ነው፡፡
• ከትውልድ ትውልድ ይህች ሀገር አንድነቷን ጠብቃ የመቆየቷ ዋናው ሚስጥር በህዝቦቿ መካከል ጸንቶ የኖረው ከዘር እና ከሃይማኖት በላይ የቆመው የመተሳሰብ ተግባር ስር ሰዶ መቆየቱ ነው፡፡
• በኢትዮጵያ ዘላቂ ዋስትና ያለው ዲሞክራሲ እንዲሰፍን ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ እድገት እንዲፋጠን በህግ የበላይነት እና በህዝቡ ፈቃድ ላይ የተመሰረተ አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ በጋራ መገንባት ያስፈልጋል፡፡
ይህን ለማሳካት የግለሰብ እና የቡድን መሰረታዊ መብቶች ያላንዳች ልዩነት እንዲከበሩ ህገመንግስቱ መሰረት ማደራጀት ያስፈልጋል፡፡
• ባለፉት አራት ወራት የተወሰዱ የእርምት እርምጃዎች የህዝቡን ጥያቄ በተወሰነ ደረጃ በመመለስ ፋታ ያስገኙ ቢሆንም መሰረታዊ የሆኑት የፍትህ ፣የዲሞክራሲ እና የህግ የበላይነት ጥያቄዎች በመመለስ ረገድ ገና ብዙ ይቀረናል፡፡
• ቀደም ባሉት አመታት በህግ ስም የመግዛት አካሄድ ያመጣቸውን መዘዞች ለማረም ከተወሰዱት ርምጃዎች መካከል አንዱ ያላግባብ ይወነጀሉ የነበሩ ዜጎችን እና የፖለቲካ ቡድኖችን ጉዳይ በይቅርታ እና በምህረት እልባት እንዲያገኝ ማድረግ ነው፡፡
• ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አንዱ የተጋረጠብን ፈተና ነጻነትን እና ስርዓት አልበኝነትን ባለመለየት መረን የለቀቀ ህግ እና ስርዓትን የማያከብር እንቅስቃሴዎች እና ድርጊቶች መስፋፋት ነው፡፡
• አሁን በሃገራችን እየታየ ያለው እና ለህግ የበላይነት ትልቁ ፈተና ለህግ ተገዥነትን ወደጎን የማድረግ ትልቅ ዝንባሌ ነው፡፡
• በስሜትና በጥላቻ የሚወሰዱ እርምጃዎች ህግን ወደራስ እጅ በመውሰድ በመንጋ የሚሰጥ የወሮበሎች ፍርድ ሲሆን ድርጊቶቹ በአንድ ክልል ፣ብሄር ፣ቋንቋ ወይም ሃይማኖት የተወሰኑ አይደሉም፡፡
እንዲህ ያሉት እንቅስቃሴዎች የዜጎችን ደህንነት እና የሃገሪቱን ሰላም በከፍተኛ ሁኔታ እየተፈታተኑ ይገኛሉ፡፡ከእንግዲህ መንግስት እንዲህ ያሉ ተግባራትን ፈጽሞ የማይታገስ መሆኑን ሁሉም ሰው ግንዛቤ ሊኖረው ይገባል፡፡
• የዜጎችን መብት እና ነጻነቶችን ለማረጋገጥ እና የአካል ፣የህይዎት እና የኑሮ ዋስትናቸውን ለማስጠበቅ ብቸኛው መሳሪያ ህግ እና ህገ-መንግስታዊ ስርዓትን በሙሉ አቅም ማስከበር ነው፡፡
• ለሃገሪቱ ህዝቦች ከመንግስት ጎን በመሆን ርብርብ ማድረግ እንዲችሉ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
• የመንግስት የጸጥታ አካላት እና ባለስልጣናትም የህግ የበላይነት በዝምታም ሆነ በድርጊት በግለሰቦች ወይም በቡድኖች ሲጣስ በቸልታ ባለመመልከት ለህግ የበላይነት መከበር በሙሉ አቅም ከህብረተሰቡ ጋር በመሆን ሊሰሩ እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

ምንጭ፣ የአማራ ብዙሃን መገናኛ