ጌታቸው ረዳን ጨምሮ የጁንታው ቡድን መሪዎች የሚጠቀሙባቸውና በአሻራ የሚከፈቱትን ጨምሮ ከ40 በላይ ተሽከርካሪዎች ተያዙ

(ኤፍ ቢ ሲ) ጌታቸው ረዳን ጨምሮ የጁንታው ቡድን መሪዎች በእግራቸው መሸሽ ከመጀመራቸው በፊት ሲጠቀሙባቸው የነበሩ ከ40 በላይ የመንግስት ተሽከርካሪዎች በመከላከያ ሰራዊቱ እጅ ገብተዋል። ቡድኑ ሰራዊቱን መቋቋም ተስኖት ወደ ገጠራማ ስፍራ በእግር መጓዝ ሲጀምር በታጣቂዎቹ በኩል ለማጥቃት ቢሞክርም እንዳልተሳካለት የ32ኛ ክፍለ ጦር አዛዥ ኮሎኔል ደጀኔ ፀጋዬ ተናግረዋል።
ፅንፈኛው ቡድን የመንገድ መሰረተ ልማት በሌለበት ከማይጨው 60 ኪሎ ሜትር ርቃ በምትገኘው ዴላ ወረዳ ከ40 በላይ የመንግስት እና በርካታ የግል ተሽከርካሪዎችን ይዞ ለመደበቅ ያደረገው ሙከራም መክሸፉን ነው ኮሎኔል ደጀኔ የተናገሩት።ተሽከርካሪዎቹን ከፅንፈኛው ቡድን ሀይሎች አስጥሎ በቁጥጥር ስር ያዋለው ሰራዊቱ ባደረገው ፍተሻ በተሽከርካሪዎቹ ውስጥ መታወቂያ እና ፓስፖርቶች ተገኝተዋል።
የተለያዩ ሰነዶቻቸውን ጥለው ከሸሹት መካከል የቀድሞው የመቐለ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ክንደያ ገብረህይወት፣ የማይጨው አስተዳዳሪ የነበረው ሀፍቱ ኪሮስ እና ሌሎች የወረዳ አመራር የነበሩ ሰዎች ሰነድ ይገኝበታል። የአካባቢው ነዋሪዎች በሰጡት ጥቆማ መሰረት ጌታቸው ረዳ በዴላ በኩል ከሸሸው ቡድን ውስጥ እንደሚገኝበትም ነው ኮሎኔል ደጀኔ የገለጹት፡፡
በመከላከያ ሰራዊቱ ከተያዙት ተሽከርካሪዎች መካከል ስድስቱ በአሻራ የሚከፈቱ እጅግ ዘመናዊ ተሽከርካሪዎች ሲሆኑ አራቱ ለኮሮና ወረርሽኝ መከላከል ስራ ከፌደራል መንግስቱ ለትግራይ ክልል የተበረከቱ አምቡላንሶች ይገኙበታል።ፅንፈኛው ቡድን ሲጠቀምባቸው የነበሩ የጭነት ተሽከርካሪዎች እና ቦቴዎችንም ሰራዊቱ ወደ ማይጨው ከተማ እንዲገቡ አድርጓል ብለዋል።በአሻራ የሚከፈቱትን ተሽከርካሪዎችም ከሞኤንኮ ጋር በመነጋገር ከአካባቢው ለማንሳትና ፍተሻ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም አውስተዋል።