ኢትዮጵያ በትግራይ የምታካሂደው ህግን የማስከበር ዘመቻ የውጭ ጣልቃ ገብነት አያስፈልገውም – በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር

  • ኢትዮጵያ በትግራይ የምታካሂደው ህግን የማስከበር ዘመቻ የውጭ ጣልቃ ገብነት አያስፈልገውም -አምባሳደር ዣኦ ዢዩአን
EBC : ኢትዮጵያ በትግራይ የምታካሂደው ህግን የማስከበር ዘመቻ የውጭ ጣልቃ ገብነት እንደማያስፈልገው አዲሱ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዢዩአን አረጋገጡ።
አዲሱ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዢዩአን የሹመት ደብዳቤያቸውን ኮፒ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሬድዋን ሁሴን አቅርበዋል።
የሹመት ደብዳቤውን ኮፒ ባቀረቡበት ወቅት በሁለትዮሽ፣ ባለብዙ ዘርፍ ግንኙነትና በጋራ ጥቅም ዙሪያ መክረዋል።
በውይይቱ ወቅትም “ኢትዮጵያ በትግራይ ክልል ህግን ለማስከበር የምታደርገው ዘመቻ የውስጥ ጉዳይ እንደሆነ ቻይና ትረዳለች” ብለዋል አምባሳደር ሬድዋን።
የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዢዩአን በበኩላቸው የኢትዮጵያ መንግስት ህግን ለማስከበር የሚያካሂደው ዘመቻ የውጭ ጣልቃ ገብነት የማያስፈልገውና በኢትዮጵያ መንግስት አቅም የሚፈታ ጉዳይ እንደሆነ አረጋግጠዋል።
የቻይና መንግስትና የቻይና የግል ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ያላቸውን የኢኮኖሚ ዘርፍ ተሳትፎ ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ተወያይተዋል።
አምባሳደር ሬድዋን ቻይና ለኢትዮጵያ ኮቪድ-19 ወረርሽኝን በመከላከል ረገድ ያደረገችውን ወሳኝ ድጋፍ አድንቀው ምስጋና አቅርበዋል።
ወረርሽኙን ለመከላከል በሚደረገው ጥረትም ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር በመተባበር እንደምትሰራ ገልጸዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ ባደረጉት ውይይትም፤ የግድቡ የድርድር ሂደት በውይይት ብቻ መፈታት እንዳለበት ተነጋግረዋል።
ለጊዜው የተቋረጠው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደቻይና የሚያደርገው በረራ ስለሚቀጥልበት ሁኔታም ተወያይተዋል።
አምባሳደር ዣኦ ዢዩአን በኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው አገራቸው ቻይናን ማገልገል መቻላቸው እንደሚያኮራቸው ገልጸዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሬድዋንም አዲሱ የቻይና አምባሳደር በኢትዮጵያ ስኬታማ ጊዜ እንደሚያሳልፉ ያላቸውን ምኞት መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።