በሐረር ከጥምቀት በዓል አከባበር ጋር በተያያዘ ትናንት እና ዛሬ አለመረጋጋት ተፈጥሮ ነበር

BBC Amharic : በሐረር ከጥምቀት በዓል አከባበር ጋር በተያያዘ ትናንት እና ዛሬ አለመረጋጋት ተፈጥሮ እንደነበር ተሰምቷል። በዚሁ ዙሪያ የሐረሪ ክልል የጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ናስር ይያ ስለተፈጠረው ነገር ማብራሪያ እንዲሰጡን ጠይቀናቸዋል።

ሐረርኃላፊውም ”የጥምቀት በዓልን ምክንያት በማድረግ የእምነቱ ተከታዮች በዓሉን ለማክበርና አካባቢውን ለማስዋብ የተለመደ እንቅስቃሴያቸውን በሚያደርጉበት ወቅት በዓሉን የማይመለከትና ሕግ የማይፈቅደውን ባንዲራ ለመስቀል ሙከራ ያደረጉ በመኖራቸው አለመረጋጋት ተከስቶ ነበር” ብለዋል።

”ይህንን ተከትሎም ትናንት የሀይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የአካባቢው ወጣቶችና ቄሮዎችን በማስተባበርና የጸጥታ ኃይሎችንም በማቀናጀት ችግር እንዳይፈጠር ማድረግ ችለናል” ሲሉ አስረድተዋል።

ኃላፊው እንዳሉት፤ አንድ ሁለት ሰዎች ሰንደቅ አላማውን ለመስቀል በሚሞክሩበት ወቅት ሌሎች ደግሞ ‘ይህን አትሰቅሉም’ በሚል ግርግር ተፈጥሮ ነበር።

”እነዚህ [ግርግሩን የፈጠሩት] ሰዎች እምነትን ከእምነት ማጋጨት፤ ሕዝብን ከሕዝብ ማጋጨት ነው እቅዳቸው። በሁሉም አካባቢዎች ታቦት በሰላም ወጥቶ ይገባል። ነገር ግን መስጂድና ቤተክርስቲያን በቅርበት በሚገኙባቸው አካባቢዎች ችግር ለመፍጠር ተሞክሯል” ብለዋል።

ዛሬ በሐረር አለመረጋጋት እንደነበርና ተኩስም እንደተሰማ በስፋት እየተነገረ መሆኑን የጠቀስንላቸው ኃላፊው፤ ጠዋት ላይ አንዳንድ ግርግሮች ተፈጥረው የነበረ ቢሆንም ከሰዓት ከተማው መረጋጋቱን መሆኑን ነግረውናል።

”ዛሬ ታቦት በሚገባበት ወቅት አራተኛ በተባለው አካባቢ ተገቢ ያልሆነ ጭፈራና ንብረት ላይ ድንጋይ መወርወር ጀምረው ነበር። አካባቢው ቤተ ክርስቲያንም መስጂድም ያለበት ከመሆኑ አንጻር በሀይማኖት ስም የተደረገው ነገር ተገቢ አይደለም። ነገር ግን ተፈጥሮ የነበረው ነገር በቁጥጥር ስር ውሏል” ሲሉ አስረድተዋል።

ንብረት ላይ ከደረሰው ጉዳት ውጪ እስካሁን የተጎዳ ሰው አለመኖሩን ኃላፊው ተናግረዋል። አቶ ናስር የጉዳት መጠኑን በትክክል ለመግለጽ ባይችሉም፤ ወደ ስምንት የሚጠጉ ቤቶች ድንጋይ ተወርውሮባቸው መስታወቶች እንደተሰባበሩ ያስረዳሉ።

ዛሬ ጠዋት ታቦት የሚሸኙ ሰዎች መንገድ ተዘግቶባቸዋል ስለመባሉ የተጠየቁት የጸጥታ ቢሮ ኃላፊው፤ ” ማንም መንገድ የተዘጋበት የለም፤ ማንም መንገድ የዘጋም የለም” ብለዋል።

”ታቦት እንዳያልፍ አልተከለከለም፤ መንገዱም ክፍት ነው። ይሄ ተግባር ውዥንብር ለመፍጠርና ሕዝቡን በእምነት ስም ለማነሳሳት የሚደረግ ጥረት ነው” ሲሉም አብራርተዋል።

ከትናንትናው እና ከዛሬው ክስተት ጋር በተያያዘ እስካሁን ሰባት ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ምዕመናን በዓሉን አክብረው ወደቤታቸው ገብተው፣ ከተማዋም ሰላማዊ እንቅስቃሴዋን እንደቀጠለች አቶ ናስር ነግረውናል።