ግለሰቦችን ወንጀል እንዲፈጽሙ ውክልና የሚሰጥ ህዝብ የለም። (ጋዜጠኛ አበበ ገላው)

በጋዜጠኛ አበበ ገላው

በየትኛውም ማህበረሰብ ውስጥ ወንጀለኞች አሉ። ወንጀል የማይፈጸምበት የአለማችን ክፍል አለ ብሎ ማመን ፈጽሞ አይቻልም። ሰው ባለበት ሁሉ መልካም ተግባርና ምግባር የመኖሩን ያህል፣ እኩይና መጥፎ ድርጊቶም በየጊዜው ይከሰታሉ።

ይሁንና የህግ የበላይነት በሰፈነበት አገር ወንጀለኞች ታድነው ለፍርድ እንዲቀርቡ ይደረጋል። እንደ አለመታደል ሆኖ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ በዘርና በሃይማኖት ተከፋፍሎ እንዲባላ የመደረጉ አንዱ ውጤት እርስ በርስ መፈራረጅ ለግለሰቦች ጥፋት ህዝብን በጅምላ ማውገዝና መክሰስ መሆኑን ዘወትር እየታዘብን ነው።

ግለሰቦችን ወንጀል እንዲፈጽሙ ውክልና የሚሰጥ ህዝብ የለም። በአንድ ክልል የሚፈጸም ወንጀል የግለሰብ ወይንም በጣት የሚቆጠሩ እኩዮች ድርጊት ከመሆን እንደማይዘል ማንም ጤነኛ አዕምሮ ያለው ሰው አይጠፋውም።

ስለሆነም የከዚህ ቀደሙም ይሁን ሰሞኑን ለተፈጸሙ አስነዋሪ ወንጀሎችም ሃላፊነት ሙሉ በሙሉ መውሰድ የሚገባቸው በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገድ መንጀሎቹን ያስፈጸሙና የፈጸሙ እኩዮች ብቻ ናቸው። ግለሰቦች ወይንም እራሳቸውን ያደራጁ ቡድኖች ለሚፈጽሙት ወንጀል ህዝብን ማውገዝ አግባብነትና የሌለው ትልቅ ስህተት ነው።

ህዝብ ወንጀል አይፈጽምም፣ ለወንጀለኞችም ውክልና ሰጥቶ አያውቅም። በመሆኑም የትኛውም ህዝብ ባላተሳተፈበት የወንጀል ድርጊት ህዝብን በጅምላ መኮነን ሊቆም ይገባል። የህግ ልእልና እንዲሰፍን ከመንግስትም ይሁን ከህዝብ የሚጠበቀው ወንጀለኞችን እየለዩ ለህግ ማቅረብ ብቻ ነው።