በሐረርጌው ጥቃት የተቃጠሉ ቤተክርስቲያናትን መልሶ ለመገንባት እንቅስቃሴ ተጀመረ

DW : ከአንድ ወር በፊት በምስራቅ እና ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች አየል ብሎ በተስተዋለው የአካባቢ ግጭት በርካታ ዜጎች ህይወት ሲያልፍ ኩርፋ ጨሌ በሚባል ወረዳ የምትገኘው ገልዲድ ማርያም እና በኩርፋ ጨሌ እና ቀረሳ ወረዳ መካከል የሚገኘው ዋቅጅራ መድኃኒለምን ጨምሮ ሶስት ያህል አብያተ ክርስትያናት መቃጠላቸው መገለፁ የሚታወስ ነው ፡፡

በአካባቢው በአብያተ ክርስትያናት ላይ የደረሰውን ጥቃት ብቻ ሳይሆን በእምነቱ ተከታዮች ላይ “ተፈፀሟል” ያለውን ጥቃት ያወገዘው የምስራቅ ሀረርጌ ሀገረ ስብከት ከውግዘት ባለፈ አብያተ ክርስትያናቱን መልሶ ለመገንባት እና የተጎዱትን ለመርዳት እንቅስቃሴ ጀምሯል ፡፡ የዚህ እንቅስቃሴ ኮሜቴ አባል በተለይ ለዶይቸ ቬለ DW በስልክ እንደገለፁት ሰሞኑን በምስራቅ ሀረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተመራ ቡድን ጉዳት የደረሰባቸውን አብያተ ክርስትያናት እና በአካባቢው ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች በአስቸጋሪ ሁኔታ ሄዶ ተመልክቷል ፡፡

በዚህም በአካባቢ ምልከታቸው ደረሰ ያሉትን ውድመት ተናግረዋል ፡፡አስተያየት ሰጪው እንዳሉት የተቋቋመው ኮሚቴ የተጎዱ ወገኖችን ለመርዳት እና በቃጠሎ የተጎዱ አብያተ ክርስትያናትን መልሶ ለመገንባት እንቅስቃሴ ላይ ሲሆን በቅርቡ በአካባቢው ለተጎዱ ወገኖች አስቸኳይ ጊዜ የሚያስፈልጉ ቁሳቆሶችን ድጋፍ ሲያደርግ የአብያተ ክርስትያናቱን መልሶ ለመገንባት ድጋፉን እያሰባሰበ ይገኛል ፡፡

Äthiopien | Orthodoxe Kirche´ in Ost-Harerge verbrannt (DW/M. Teklu) በአካባቢው ጉዳት የደረሰባቸውን አብያተ ክርስትያናት መልሶ ለመገንባት እየተሰባሰበ ስላለው እንስቃሴ እና ከመልሶ ግንባታው ጋር በተያያዘ ጥያቄ ያቀረብኩላቸው አስተያየት ሰጪ ተከታዩን ብለዋል ፡፡በአካባቢው በቅርቡ የተከሰተው ግጭት እና የተፈፀመው ጥቃት ከፍተኛ ነው ያሉት አስተያየት ሰጭው በቀጣይ መልሶ ግንባታ ለማከናወን እና ተጎጅዎችን መልሶ ማቋቋምም መሰል ጥቃቶች እንዳይፈፀሙ በአሁኑ ጉብኝት ከአካባቢውም ሆነ ከሌሎች የሚመለከታቸው ባለስልጣናት ጋር መነጋገራቸውንና በአንዳንድ ወረዳ አመራሮች እየተከናወነ ያለው ተግባርም የሚያስመሰግን መሆኑን ገልፀዋል ፡፡በሰሞኑ ግጭት የደረሰውን ጉዳት እና ጥፋት መልሶ ለማቋቋም የሚደረገው ጥረት ይኑር እንጂ አሁንም ከእነዚሁ አካበባቢዎች ተፈናቅለው የሚገኙ ዜጎችን መልሶ ማቋቋም የሁሉንም ጥረት የሚጠይቅ ስለመሆኑ አስተያየት የሚሰጡ አሉ፡፡