አርባ በመቶ ዕፀዋቶቿን ኢትዮጵያ ልታጣ እንደምትችል ተነገረ

BBC Amharic : ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ የአፍሪካ አገራት ከ40 በመቶ በላይ የዕፀዋት ሃብታቸውን ሊያጡ እንደሚችሉ አንድ ጥናት አመለከተ።

ከኢትዮጵያ በተጨማሪም በርካታ የምዕራብ አፍሪካ አገራት ታንዛኒያና ዴሞክራቲክ ኮንጎ ከአንድ ሦስተኛ በላይ ተፈጥሮ የለገሰቻቸውን የዕፀዋት ሃብታቸውን ያጣሉ ተብሏል።

የመጥፋት አደጋ ከተጋረጠባቸው የዕፀዋት ዝርያዎች መካከል ዛፎች፣ ሃረጎች፣ የመድሃኒት ዕፀዋትና ሌሎችም የተፈጥሮ ሃብቶች ናቸው ተብሏል።

ሳይንቲስቶች እንዳሉት ለእነዚህ ዕፅዋት መጥፋት አደጋን የደቀኑት በአገራቱ ውስጥ ያለው ከፍተኛ የደን ምንጣሮ፣ የህዝብ ቁጥር መጨመርና የአየር ሁኔታ ለውጥ ናቸው።

“የተፈጥሮ ብዘሃ ሕይወት ለሰው ልጆች ተገልጸው የማያልቁ ጥቅሞችን የሚያበረክቱ ሲሆን፤ የእነሱ መጥፋት ደግሞ የምድራችንን ቀጣይነት አደጋ ላይ ይጥለዋል” ሲሉ በፈረንሳይ ብሔራዊ የዘላቂ ልማት ተቋም ውስጥ አጥኚ የሆኑት ዶክተር ቶማ ኩቭረር ተናግረዋል።

የብዝሃ ሕይወት ሃብቶች መጥፋት በተለይ በትሮፒካል የአየር ንብረት ክልል ውስጥ በሚገኙ የአፍሪካ አገራት ላይ ከባድ ችግርን ይጋርጣል። “በዚህ አካባቢ አስደናቂ የብዘሃ ሕይወት ሃብት ቢኖርም ነገር ግን የሚስተዋሉት ወሳኝ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ችግሮች እንዲሁም በመጪዎቹ አስርት ዓመታት ከሚጠበቀው የሕዝብ ቁጥር መጨመር ጋር ተዳምሮ ጉዳቱን ያከፋዋል” ብለዋል።

‘ሳይንስ አድቫንስስ’ በተባለው የሳይንሳዊ ጥናት መጽሔት ላይ የወጣው የባለሙያዎቹ ምርምር ውጤት ለመጥፋት የተጋለጡ የተፈጥሮ ሃብቶችን ለማወቅ ተከልሶ የተዘጋጀን የጥናት ዘዴን መሰረት አድርጎ የተሰራ ነው።

ከዕፅዋቱ በተጨማሪ በጥናቱ እስካሁን ድረስ ከ10 አጥቢ እንስሳት ዘጠኙ እንዲሁም ከአእዋፋት መካከል ደግሞ ሁለት ሦስተኞቹ ጥናት ተደርጎባቸዋል። ከዕፅዋት መካከልም ከስምንት በመቶ በታች የሚሆኑት፣ ውሃና ድንጋይ ላይ የሚበቅሉ የአልጌ ዝርያዎችን ሳይጨምር፣ የሚያብቡና ሌሎች ዕፅዋትን ጥናቱ ተመልክቷል።

ተመራማሪዎቹ 20 ሺህ የሚሆኑ የመጥፋት አደጋ የተጋረጠባቸውን የዕፅዋት ዝርያዎች ላይ፣ ተመሳሳይ ግን በጣም የተፋጠነ ዘዴን ተጠቅመው ጥናታቸውን አካሂደውባቸዋል።

በጥናታቸውም 33 በመቶ የሚሆኑት ዝርያዎች ከፍተኛ የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠባቸው ሲያመለክቱ በብዛት ከማይገኙ ሌሎች ዝርያዎች መካከል ደግሞ አንድ ሦስተኛው በቅርቡ የመጥፋት የስጋት ምድብ ውስጥ ሊገቡ እንደሚችሉም ተጠቁሟል።

ለዚህ ሁሉ የዕፅዋት መጥፋት ስጋት እንደምክንያት በአብዛኛው የሚጠቀሱት የደን መመንጠር፣ በመሬት አጠቃቀም ላይ የታዩ ለውጦች፣ የሕዝብ ቁጥር መጨመርና የአየር ንብረት ለውጥ በቀዳሚነት በአጥኚዎቹ ተጠቅሰዋል።