የህወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጋር ያደረጉት ውይይት ውጤታማ አልነበረም ተባለ

BBC Amharic : ቅዳሜ ኅዳር 7/ 2012 ዓ.ም በተካሄደው የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ግንባሩ ወደ ውህደት እንዲያመራ በአብላጫ ድምጽ ሲወሰን ስድስት የህወሓት ተወካዮች የተቃውሞ ድምጽ ሰጥተው ነበር።

በቀጣዩ ቀን ዕሁድም በተካሄደው ስብሰባ ላይ የህወሓት አባላት ያልተሳተፉ ቢሆንም ከኢህአዴግ ሊቀመንበር ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ ጋር የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አባላት ተገናኝተው ሊወያዩ እንደሆነ ቢቢሲ የህወሓት ከፍተኛ አመራር አባል የሆኑትን አቶ አስመላሽ ወልደሥላሴን ጠቅሶ ዘግቦ ነበር።

እንደተባለውም ጠቅላይ ሚኒስትሩና የህወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በኢህአዴግ የውህደት ሂደት ላይ በተፈጠረው የአቋም ልዩነት ላይ መወያየታቸውን ለግንባሩ ቅርብ የሆኑ ምንጮች ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።

ቢቢሲ ዛሬ ማክሰኞ ከህወሓት ጽሕፈት ቤት ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው የግንባሩን ውህደት በተመለከተ የህወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጋር እሁድ ዕለት ያደረጉት ውይይት ውጤታማ ሳይሆን እንደቀረ ያመለክታል።

በውይይቱ ላይም በኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ቅዳሜ ዕለት ከተሳተፉት ስምንት አባላት መካከል አንደኛው በሥራ ጉዳይ ወደ መቀሌ በመሄዳቸው ምክንያት ሰባቱ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በተደረገው ውይይት ላይ እንደተሳተፉ ተነግሯል።

ምን ተወያዩ፤ ውጤቱስ?

ቢቢሲ ውይይቱን በተመለከተ ከህወሓት ጽህፈት ቤት ያገኘው መረጃ የህወሓት አባላት በጉዳዩ ላይ ደግመው እንዲያስቡበትና ከግንባሩ ጋር አብረው እንዲሰሩ ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጥያቄ ቀርቦላቸው እንደነበረ ያመለክታል።

ይሁን እንጂ በቅዳሜው ስብሰባ ላይ የተሳተፉት የህወሓት ሥራ አሰፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ቀደም ሲል በውህደቱ ጉዳይ ላይ ከያዙት አቋም ውጪ የሚቀይሩት ነገር እንደሌለ በመግለጽ በውሳኔያቸው ስለጸኑ ውይይቱ የተጨበጠ ፍሬ ሳይገኝ ማብቃቱ ተገልጿል።

እስከ ትናንት [ሰኞ] ድረስ ለሦስት ቀናት የቀጠለው ኢህአዴግና የአጋር ድርጅቶቹ የግንባሩን ውህደት በተመለከተ ሲያካሂዱት የነበረውን ስብሰባ አጠናቀው ጉዳዩን ለድርጅቱ ምክር ቤት እንዲቀርብ መወሰናቸው ተገልጿል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድም በማህበራዊ መገናኛ መድረኮች ላይ እንዳሰፈሩት በሚዋሃደው ፓርቲ ሕገ ደንብ ላይ እንደተወያዩና እንዳጸደቁት ጠቅሰው ሰንወያይ “ወደ ምክር ቤቱ እንዲመራ ወስነናል” ብለዋል።

አክለውም “የሦስቱም ቀናት ውይይታችን ግልጽና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መልኩ ተካሂዷል። ውይይቱ ይበልጥ አመራሮቹን ያቀራረበ ሆኖ በመጠናቀቁ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል” ሲሉ ውይይታቸው በመግባባት መጠናቀቁን ጠቅሰዋል።

ከዚህ በኋላ ህወሓት፣ ቀሪዎቹ የግንባሩ አባላትና አጋር ድርጅቶች በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በኩል ሂደቱ ስላለቀ በቀጣይ በሚካሄደው የኢህአዴግ ምክርቤት መድረክ በውህደቱ ላይ ሊወያዩ እንደሚችሉ ይጠበቃል።

ለረዥም ግዜ ሲመከረበትና ሲጠና የቆየው የኢህአዴግ የውህደት ጉዳይ ላይ ሌሎቹ የግንባሩ አባላትና አጋር ድርጅቶች የደገፉት ሲሆን፤ ህወሓት ግን በነበረው የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ፕሮግራም መቀጠል አለብን በማለቱ ነው ልዩነቱ የተፈጠረው።

ህወሓት ግንባሩን የማዋሃዱ ጥረት “አሃዳዊ ሥርዓት ለመፍጠር እና በስልጣን ላይ ለመቆየት የሚደረግ መሆኑ ሲናገር” ውህደቱን የሚፈልጉት ደግሞ “ከለውጡ ጋር የሚሄድ አዲስ ፕሮግራም አስፈላጊ” መሆኑን ይጠቅሳል።

ጠቅላይ ሚኒስተር ዐብይ አህመድ እና ሌሎች የውህደቱ ደጋፊ የደርጅቶች አመራሮች በበኩላቸው ውህደቱ አሀዳዊ ሥርዓትን የማያመጣና ሕብረ ብሔራዊ ፌደራሊዝሙን የሚያስቀጥል እንደሚሆን በመጥቀስ የውህደቱ ጠቀሜታ ይጠቅሳሉ።

ቢቢሲ የኢህአዴግ ሊቀመንበር በሆኑት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድና በህወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት መካከል የነበረውን ውይይት በተመለከተ መረጃ ለማግኘት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤትን ቢጠይቅም ጉዳዩ የግንባሩ ጽህፈት ቤት መሆኑ ተገልጾለታል።

በተጨማሪም ከኢህአዴግ ጽህፈት ቤት መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካልንም።