BBC Amharic : ትላንት በድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ፤ ሴት ተማሪዎች በመንግሥት ሆስፒታል የእርግዝና ምርመራ አድርገው በ48 ሰዓት ውስጥ ለፕሮክተራቸው (ለተቆጣጣሪዎች) እንዲያስገቡ የሚያሳስብ ማስታወቂያ መውጣቱ በርካቶችን አነጋግሯል።
ዩኒቨርሲቲው “ማስታወቂያው የወጣው በስህተት ነው” ሲል ማስተባበያ ቢያወጣም፤ ማስታወቂያው ለምን እና እንዴት ወጣ? ተማሪዎች እንዲመረመሩ ማስገደድ ሕጋዊ አግባብ አለው? በዩኒቨርስቲው ተማሪዎች በተደጋጋሚ ስለመውለዳቸው እና ህጻናት ተጥለው ስለመገኘታቸው የሚናፈሰው እውነት ነው? የሚሉና ሌሎችም ጥያቄዎች እየተሰነዘሩ ነው።
ማስታወቂያው የወጣው በተማሪዎች ኅብረት እንደሆነ የሚገልጸው የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ የተማሪዎች ኅብረት ፕሬዘዳንት ዳንኤል ጌታቸው፤ “ጠዋት ላይ [ሕዳር 28 ቀን 2012 ዓ. ም.] ውይይት ሳይኖር [በተማሪዎች ኅብረትና በዩኒቨርስቲው መካከል] በስሜታዊነት የተደረገ ነው፤ ስህተት መሆኑን አምነን ይቅርታ ጠይቀናል” ሲል ተናግሯል።
በእለቱ ጠዋት ልጅ ወልዳ መንገድ ዳር ጥላ የሄደች ተማሪ እንደነበረች የሚናገረው ዳንኤል፤ ክስተቱ ስሜታዊ እንዳደረጋቸው ገልጾ፤ ይህን ተከትሎ ማስታወቂያው የወጣው “ነገሩ ስላሳሳበን ነው” ይላል።
የተባለው ችግር በዩኒቨርስቲው አለ ቢባል እንኳን፤ የእርግዝና ምርመራ ይደረግ ብሎ ማስገደድ እንዴት መፍትሔ ይሆናል? ብለን ላቀረብንለት ጥያቄ፤ “ሌሎች ሴቶች ላይ እንዳይከሰት አስበን ነው፤ ባለማስተዋል የተደረገ ነው” ሲል መልሷል።
በዩኒቨርስቲው ተማሪዎች በተደጋጋሚ ይወልዳሉ? ህጻናት ተጥለው ስለመገኘታቸው የሚናፈሰው ወሬስ እውነት ነው? ብለን ጥያቄ ያቀረብንላቸው የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ት መቅደስ ካሳሁን “ምን ያህል አለ? እስከዛሬ ምን ተሠራ? የሚለው መረጃ ተሰብስቦ እየተሠራ ነው። ሠርተን ይፋ እናደርጋለን” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
የተማሪዎች ኅብረት፣ የተማሪዎች ዲን እና ፕሮክተሮች፤ ዩኒቨርስቲው ላይ እውን ይሄ ነገር ይደጋገማል ወይ? ከሌሎች ዩኒቨርስቲዎች ምን የተለየ ነገር አለ? የሚለውን መረጃ በመሰብሰብ እየሠሩ መሆኑንም አክለዋል።
ትላንት የወጣውን ማስታወቂያ በተመለከተ “ማስታወቂያ ወጥቷል። ግን የወጣው ኦፊሻል አይደለም። እኛ አስተባብበለን በኦፊሻል ገጻችን ላይ አውጥተናል” ብለዋል ወ/ት መቅደስ።
የሕግ ባለሙያዋ ወ/ሮ ሰብለ አሰፋ በበኩላቸው፤ ዩኒቨርስቲው ማስታወቂያው ኦፊሻል አይደለም ሲል ቢያስተባብልም፤ የተማሪዎች ኅብረት የአስተዳደሩ አካል በመሆኑ ይህን ማለት አይችልም ይላሉ።
“አስተዳደሩ በሥሩ ያሉ ተማሪዎችን ያለ ፍቀዳቸው አገድዶ የህክምና ምርመራ እንዲያደርጉ የማድርግ ሥልጣን የለውም። ተማሪዎቹ በአንድ ማስታወቂያ ይህን እንዲያድረጉ በማዘዝ ያወጣው ነገር ሥልጣንን ያላግባብ መጠቀም ነው” ሲሉ ያስረዳሉ።
በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ድንጋጌ እንዲሁም በኢትዮጵያ ሕግም፤ አንድ ግለሰብ ያለፈቃዱ የህክምና ምርመራ እንዲያደርግ እንዳይገደድ በሕግ ጥበቃ የማግኘት መብት እንዳለው ጠቅሰዋል።
“አስተዳደሩ ተማሪዎች ምርመራውን እንዲያደርጉ ያወጣው ማስታወቂያ ግልጽ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው። ግልጽ የሆነ የሕግ ድንጋጌዎችን የሚጻረርም ነው” ብለዋል።
የትኛውም ምክንያት ቢኖር ሰውን አስገድዶ ምርመራ ማስደረግ ኢ-ሰብአዊ እና ጭካኔ የተሞላበት እንደሆነ ወ/ሮ ሰብለ ይገልጻሉ።
ዩኒቨርስቲው ውስጥ ተማሪዎች ወልደው ልጅ ስለመጣላቸው ቢነገርም፤ የተረጋገጠ መረጃ አለመሆኑን ጠቅሰውም፤ ይህ ተከስቶ ቢሆን እንኳን አደረጉ የተባሉ ተማሪዎችን በአግባቡ አጣርቶ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ ይናገራሉ።
መላው የዩኒቨርስቲውን ሴት ተማሪዎች አስገድዶ ተመርመሩ ማለት “ሴት ተማሪዎችን መፈረጅ ነው” ሲሉም ያክላሉ።
የሕግ ባለሙያዋ “በመረጃ ላይ የተመሰረተ መሆኑን ባናውቅም ሆነ የተባለው ነገር ሲሰማ ከባድ ነው። ግን ሴት ተማሪዎችን ባጠቃላይ ተመርመሩ ማለት፤ ሁሉም ሴቶች ያላግባብ፣ ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ እያረገዙ መሬት ላይ ልጅ ይጥላሉ በሚል የሚፈርጅ ነው። ሴት ተማሪዎች ሆነው እዚያ በመገኘታቸው ብቻ በቡደን፣ በመጥፎ ሁኔታ የሚፈርጅ ነው” በማለትም ያብራራሉ።