ፌስቡክና የማኅበራዊ ድረ-ገፆች ሚና በኢትዮጵያ ምርጫ – ውይይት

DW : ኢትዮጵያ በ2012 ዓ.ም. በምታካሒደው ምርጫ ፌስቡክን የመሳሰሉ ማኅበራዊ ድረ-ገፆች እና ተጽዕኖ ፈጣሪ የሆኑ የለውጥ አራማጆች (activists) ምን አይነት ሚና ይኖራቸዋል? የኢትዮጵያ ተቋማት የምርጫውን ፍትሐዊነት፣ ነፃነት እና ተዓማኒነት ለማስጠበቅ በማኅበራዊ ድረ-ገፆች የሚሰራጩ ሐሰተኛ መረጃዎችን የሚቆጣጠሩበት ሥርዓት ከወዴት አለ?

ባለፈው አንድ አመት ተኩል ገደማ ፌስቡክን ጨምሮ ማኅበራዊ ድረ-ገፆች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ያላቸው ሚና ግዘፍ ነስቶ ተፅዕኖ ማሳደር ጀምሯል። የመንግሥት ተቋማት፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ባለሥልጣናት እና ራሳቸውን የለውጥ አራማጅ (activists) ብለው የሚጠሩ ግለሰቦች የግል አስተያየታቸውን አሊያም መረጃዎቻቸውን ፌስቡክ እና ትዊተርን በመሳሰሉ ማኅበራዊ ድረ-ገፆች ያሰራጫሉ። የተረጋገጡ መረጃዎች፤ ጠቀሜታ ያላቸው ክርክሮች የመኖራቸውን ያክል በማኅበረሰቦች እና በሐይማኖቶች መካከል መቃቃር ግፋ ሲልም ግጭት ሊቀሰቅሱ የሚችሉ አስተያየቶች፤ ዘለፋዎች እና ሐሰተኛ መረጃዎችም በእነ ፌስቡክ መንደር ይታያሉ።

በሚሊዮኖች እና በመቶ ሺሕዎች የሚቆጠሩ ተከታዮች ያሏቸው የለውጥ አራማጆች በ2012 ዓ.ም. ይካሔዳል ተብሎ በሚጠበቀው ምርጫ ምን አይነት ሚና ይኖራቸዋል? የኢትዮጵያ የመንግሥት ተቋማት የምርጫውን ነፃነት፤ ተዓማኒነት እና ፍትኃዊነት ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድሩ የሚችሉ የማኅበራዊ ድረ-ገፆች መረጃጃዎችን የሚቆጣጠሩበት ሥርዓት ይኖር ይሆን?

አቶ ያሬድ ኃይለማርያም የስብስብ ለሰብአዊ መብት በኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ፤ ዶክተር እንዳልካቸው ጫላ በአሜሪካ ሚኒሶታ የሐምሊን ዩኒቨርሲቲ የኮምዩንኬሽን ጥናት መምህር እንዲሁም ዶክተር ሙከርም ሚፍታህ በቱርክ አንካራ የማኅበራዊ ሳይንስ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ ጥናት የትምህርት ማዕከል መምህር በውይይቱ ተሳትፈዋል።DW