በአዲስ አበባ በአንድ ወር ውስጥ 7 የኤሌክትሪክ ትራንስፎርመሮች ተሰርቀዋል ተባለ

በአዲስ አበባ በተለያየ ጊዜ እና ቦታ በአንድ ወር ውስጥ 7 የኤሌክትሪክ ትራንስፎርመሮች መሰረቃቸውን የከተማው ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለ ዶይቼ ቬለ « DW » አረጋገጠ። ዕቃዎቹ በሦስት የተለያዩ አካባቢዎች የተዘረፉ ሲሆን ከዚህም መካከል ከባድ የዕቃ መጫኛና ማውረጃ ተሽከርካሪ ተጠቅመው አገልግሎት ይሰጥ የነበረን ትራንስፎርመር ሲያወርዱ እጅ ከፈንጅ የተያዙ ይገኙበታል። ከተሰረቁት ትራንስፎርመሮች መካከል አምስቱ እስካሁን የደረሱበት አለመታወቁን እና ወንጀለኞችም አለመያዛቸውንም በአገልግሎቱ የኮሙኑኬሽን ሥራ አስኪያጁ አቶ በቀለ ክፍሌ ተናግዋል። በመሥሪያ ቤቱ የኤሌትሬክ ገመድ ቆረጣ እና ስርቆት እንጅ እንዲህ ያለው ድርጊት አጋጥሟቸው እንደማያውቅ ጠቅሰው ፣ ክስተቱ ግን በተጠናና የዕቃውን ሁኔታና ጥቅም ብሎም ውስጡን በሚያውቅ አካል ሳይፈጸም እንዳልቀረ ግምታቸውን ተናግረዋል። በተቋሙ በርካታ ቁጥር ያላቸው ትራንስፎርመሮች በብልሽት ተቀምጠው እንደሚገኙም ተናግረዋል።