በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሰላም መደፍረስና አለመረጋጋቶች ይታያሉ።

DW – በኢትዮጵያ በቅርቡ የተጀመረዉን የፖለቲካ ለዉጥ ተከትሎ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሰላም መደፍረስና አለመረጋጋቶች ይታያሉ። ይህንን ተከትሎ ብሄራዊ ዕርቅና መግባባትን ለመፍጠር መንግስት የተለያዩ ርምጃዎችን እየወሰደ ቢገኝም ችግሩ አሁንም ድረስ እልባት ያገኜ አይመስልም። 

በኢትዮጵያ  የፖለቲካ እስረኞች መፈታታቸዉ ፣የተለያዩ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም ያላቸዉ የፖለቲካ ድርጅቶች በነፃነት ሀሳባቸዉን ማራመድና በሀገሪቱ መንቀሳቀስ መጀመራቸዉ፣ የመገናኛ ብዙሃን ነፃነትና መንግስት ከዚህ ቀደም ይወቀስባቸዉ የነበሩና አፋኝ ይባሉ የነበሩ ህጎች ላይ ማሻሻያና ለዉጥ መደረጉ በለዉጡ የተገኙ ፍሬዎች ቢሆኑም የሰላምና የፀጥታ ጉዳይ  በሀገሪቱ አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ብዙዎች ይናገራሉ።
ይህንን ችግር  ለመፍታት መንግስት የተለያዩ የሰላምና የፀጥታና ኮንፍረንሶችን በየ አካባቢዉ እያካሄደ ይገኛል። ያም ሆኖ ግን ችግሩን የፈቱት አይመስልም።  በተለይ በማህበራዊ መገኛኛ ዘዴዎች ጎራ ለይቶ የእኛ እና የእነሱ የሚሉ ዉዝግቦች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ ሔደዋል። የዜጎች መፈናቀል ፣ስርዓት አልበኝነትና ህገ ወጥነትም ከለዉጡ ወዲህ በተደጋጋሚ የሚሰሙ ጉዳዮች ሆነዋል።ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ምን መደረግ አለበት በሚል DW ያነጋገራቸዉ በሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች  ባለሙያና አማካሪ  የሆኑት አቶ ሚናስ ፍስሃ  ይህ መሰሉ ችግር በለዉጥ ሂደት የሚጠበቅ ነዉ።ችግሩ የሚመነጨዉም መንግስት መስራት የሚችልበት አቅምና የህብረተሰቡ ፍላጎት አለመመጣጠን ነዉ ይላሉ።
ለዚህም  መንግስትን ሊያግዙ የሚችሉ የዲሞክራሲ ተቋማትን በሀገሪቱ መገንባት ችግሩን በዘላቂነት ይፈታዋል ባይ ናቸዉ።

በሀገሪቱ አሁን በተፈጠረዉ ዕድል በነፃነት እንዲንቀሳቀሱ የተፈቀደላቸዉ የሲቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶችም ህብረተሰቡን ወርደዉ በማወያየትና ችግሮችን በመለየት ለዘላቂ ሰላም ሊሰሩ ያስፈልጋልም ብለዋል።የሀይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎችም በአካባቢያቸዉና በማህበረሰቡ ዘንድ  ያላቸዉን ተሰሚነት በመጠቀም ስለ ሰላምና አብሮነት ቢሰብኩ የተሻለ ዉጤት ሊገኝ እንደሚችል ባለሙያዉ አስረድተዋል።

ያም ሆኖ ግን በክልሎች መካከል የሚታየዉ የትብብር መንፈስ መቀዛቀዝና  በጥርጣሬ መተያየትም በኢትዮጵያ አሁን እየታየ ላለዉ የሰላምና የፀጥታ ችግር ሌላዉ ምክንያት መሆኑ ይነገራል።በቅርቡ የአማራና የትግራይ ክልሎች ያወጧቸው መግለጫዎች የዚህ  ማሳያ ነዉ የሚሉ አሉ። በወልቂጤ ዩንቨርሲቲ የፓለቲካል ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ዳንኤል መኮነን በዚህ ሀሳብ ይስማማሉ።እሳቸዉ እንደሚሉት አብዛኛዉ ያለመረጋጋትና የሰላም ችግር የመጣዉ ሀገሪቱን እየመራ ባለዉ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች መካከል ስምምነት አለመኖር ነዉ።
ይሁንና ችግሩ የተለያዩ መፍትሄዎች ቢኖሩትም በዋናነት መፍትሄዉ ፖለቲካዊ ነዉ ይላሉ።